ከሐምሌ 1-8/2018 ዓ.ም በጄኔቫ ስዊዘርላንድ እየተካሄደ በሚገኘው 68 ኛው የዓለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት (WIPO) ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ የአእምሯዊ ንብረት ሥርዓት ያላትን ጽኑ ቁርጠኝነት በድጋሚ አረጋግጣለች፡፡

የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ክቡር አቶ ወልዱ ይመሰል ባራኪ ባደረጉት ንግግር፤ ሀገሪቱ ፈጠራን፣ አርቲስቲክ ስራዎችን እና ዘላቂ ልማትን ለማበረታታት እያደረገች ያለቸው ቀጣይነት ያለው የሕግና የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ጎልቶ ተገልጿል፡፡
ክቡር አቶ ወልዱ የዓለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዳረን ታንግ ለሁለተኛ የሥራ ዘመን በመመረጣቸው የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን በመጀመሪያው የሥራ ዘመናቸው ኢትዮጵያ በአእምሯዊ ንብረት ዘርፍ የተሻለ ደረጃ እንድትደርስ ላደረጉት አመራርና ቀጣይነት ያለው ድጋፍ አመስግነዋል፡፡ በተያያዘም ዋና ዳይሬክተሩ ባለፈው ዓመት በኢትዮጵያ ያደረጉትን ጉብኝት አድንቀዋል፡፡

ክቡር አቶ ወልዱ ኢትዮጵያ የአእምሯዊ ንብረት ማዕቀፏን በማዘመን፣ ቁልፍ በሆኑ ዓለም አቀፍ የአእምሯዊ ንብረት ስምምነቶች ላይ ለመሳተፍ የምታደርገውን ጥረት በማፋጠን፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና (AfCFTA) የአእምሯዊ ንብረት ፕሮቶኮል ትግበራን በመደገፍ እና የዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) ኢትዮጵያ ከአእምሯዊ ንብረት ድርጅት (WIPO) ጋር ያላትን አጋርነት ይበልጥ ለማጠናከር ያለባትን ቁርጠኝነት በድጋሚ በማረጋገጥ፣ አእምሯዊ ንብረት ለኢኮኖሚ ሽግግር፣ ለኢንቨስትመንት፣ ለኢንዱስትሪ ልማት እንዲሁም ለፈጠራ፣ ለሀገር በቀል እውቀትና ለባህላዊ ቅርሶች ጥበቃ የሚረዳ ስትራቴጂካዊ መሣሪያ መሆኑን ገልጻለች፡፡
(በጉባኤው ጎን ለጎን የብሪክስ (BRICS) አባል ሀገራት የአእምሯዊ ንብረት ተቋማት ኃላፊዎች ተገናኝተው በአእምሯዊ ንብረት ዘርፍ ስላደረጓቸው ለውጦች የተወያዩ ሲሆን፣ ከነሐሴ 26 እስከ 28 ቀን 2018 ዓ.ም በሕንድ ሀገር ለማካሄድ በታቀደው ቀጣይ የኃላፊዎች ስብሰባ አጀንዳ ላይ ተስማምተዋል፡፡ ኢትዮጵያ በውይይቱ ላይ እንደ ብሪክስ አባልነቷ የተሳተፈች ሲሆን፣ በብሪክስ አባል ሀገራት መካከል ያለውን የአእምሯዊ ንብረት ትብብር ለማጠናከር ያላትን ቁርጠኝነት በድጋሚ አረጋግጣለች፡፡