የአለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት፣ የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣንና ጎንደር ዩኒቨርስቲ በትብብር ያዘጋጁትና ትኩረቱን የባህላዊ ህክምና ዕውቀት ጥበቃ እና ግብይት ያደረገ ብሄራዊ የግንዛቤ ማሳደጊያ ወርክሾፕ ዛሬ መጋቢት 11፣2015 ዓ·ም በአዳማ ናፍሌት ሆቴል ተካሄደ።
አምስተኛ ዙር በሆነው በዚሁ ወርክሾፕ የባለስልጣኑ ሃላፊዎችና ባለሙያዎች ፣ የዩኒቨርስቲው የዘርፉ ምሁራን፣ የድሬደዋና ሀረሪ ክልል ጤና ቢሮ ተወካዮችና የባህል ህክምና ባለሙያዎች ተካፋዮች ሲሆኑ በአለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት በማደግ ላይ ያሉ ሃገራት ዲቪዥን ዳ/ር ሚስተር ዙንግ፣ የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳ/ር ኤርሚያስ የማነብርሃን (ፒኤችዲ) እና የጎንደር ዩኒቨርስቲ የማ/ብ አቀፍ አገልግሎትና ቴክኖሎጂ ሽግግር ቺፍ ዳ/ር ፕሮፌሰር ታደሰ ወርቁ የመክፈቻ ንግግር አድርገዋል።
የባህል ህክምና ዕውቀት ጥበቃ ፓይለት ፕሮጀክት በኢትዮጵያ፣ አሁናዊ የኢትዮጵያ የባህል ህክምና ዘርፍ እድገት፣ አእምሯዊ ንብረት እና የማህበረሰብ ዕውቀት በኢትዮጵያ እና ሌሎችም ርዕሰ ጉዳዮች ቀርበው ውይይት የተደረገ ሲሆን የባህል ህክምና አዋቂዎች የልምድ ልውውጥ ንግግር አድርገዋል። በባህል ህክምና አዋቂዎቹ የተቀመሙና እሴት የተጨመረባቸው የባህል መድሃኒቶች ቀርበው ለተሳታፊዋች ገለፃ ቀርቧል።

እስካሁን በተካሄዱ የሥልጠና መድረኮችና የግንዛቤ መሻሻሎች 47 የባህል ሀኪሞች የሰርቪስ ማርክ/ንግድ ምልክት ማመልከቻ ማቅረብ የቻሉ መሆኑና ለ31ዱ ሰርተፊኬት እንደተሰጣቸው ተገልጿል። ባለሙያዎቹ በአእምሯዊ ንብረት ጥበቃ ሥርዓት መመራታቸውና ለዘርፉ ትኩረት ተሰጥቶት እያገኙ ያሉት ስልጠናና ድጋፍ ዘርፉን ለማሳደግ እየጠቀመ መሆኑን አስረድተዋል።