የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት እና የአውሮፓ ፓተንት ጽ/ቤት በዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመስራት ያደረጉትን የሁለትዮሽ ስምምነት ተከትሎ ትናንት ጳጉሜ 3 ቀን 2013 ዓ.ም የፓተንት ምርመራ ባለሙያዎች የመክፈቻ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡
የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት ዋና ዳይሬክተር ኤርሚያስ የማነብርሃን በመርሃ ግብሩ የመክፈቻ ንግግራቸው የፓተንት ምርመራ ባለሙያዎችን አቅም ለመገንባት በእጅጉ የሚረዳውን ስልጠና እውን እንዲሆን ያደረጉትን የአውሮፓ ፓተንት ጽ/ቤትን እና የአፍሪካ ክልላዊ የአእምሯዊ ንብረት ድርጅትን አመስግነዋል፡፡
የአውሮፓ ፓተንት ጽ/ቤት ልዑካን በ2011 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ከኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት ጋር በህግ ማርቀቅ ላይ የቴክኒክ ድጋፍ፣ በዘመናዊ የመረጃ አያያዝና የመረጃ ልውውጥ እንዲሁም በአቅም ግንባታ እና ተያያዥ ስራዎች ላይ በትብብር ለመስራት ፍሬያማ ውይይት ካደረጉበት ወቅት ጀምሮ ተጠናክሮ የቀጠለ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሩ አክለው ገልፀዋል፡፡
በ18 ወሩ የፓተንት ምርመራ ባለሙያዎች ስልጠና ከአፍሪካ ክልላዊ የአእምሯዊ ንብረት ድርጅት፣ ከኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት እና ከአንጎላ ኢንዱስትሪያዊ ንብረት ኢንስቲትዩት የሚወከሉ ከ100 በላይ ሰልጣኞች እንደሚሳተፉ ተገልፆል፡፡