የዓለም አእምሯዊ ንብረት ቀን #WorldIPDay በሀገራችን ሚያዝያ 20-21/2014ዓ.ም በኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ግቢ ውስጥ በድምቀት ተከብሯል።
የዘንድሮው የዓለም አእምሯዊ ንብረት ቀን አከባበር በታዳጊና በወጣት ፈጣሪዎችና ተመራማሪዎች ላይ ትኩረት በማድረግ በኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ፣ በኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ እና በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ትብብር እምቅ አቅም ያላቸውን 61 ታዳጊዎችና ወጣቶች ወደፊት ለማምጣት እና ለማበራከት ስራዎቻቸውን በተዘጋጀው አውደ ርዕይ ላይ እንዲያቀረቡ የተደረገ ተደርጓል ። አዉደ ርዕዩ ሀሙስ ሚያዝያ 20/2014 ዓ.ም በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሚንስቴር ሚንስትር ክቡር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በተገኙበት ለጎብኚዎች ክፍት ሆኖ ለሁለት ቀናት ተጎብኝቷል።
ክቡር ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክትም የቴክኖሎጂ ሽግግርን የሚደግፉ ፈጠራዎች ተግባራዊ እንዲሆኑ ሚንስቴር መ/ቤቱ እንደሚያበረታታ በመግለጽ ጠንካራ የአእምሮአዊ ንብረት ስርዓት በመመስረት አእምሯዊ ንብረት የልማት መሳሪያ እንዲሆን ዓለም አቀፋዊ እና ሀገራዊ የዕድገት ደረጃዎችን ያማከለ የአእምሯዊ ንብረት ፖሊሲን የማዘጋጀትና ተግባራዊ የማድረግ ስራው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በማሳሰብ ለስኬታማነቱም ሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸው ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡










በዛሬ የመዝጊያ መርሀግብር የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኤርምያስ የማነብርሀን (ዶ/ር) እና የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ኤክስክዩቲቭ ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ተከተል ዮሀንስ ለፈጠራ አቅራቢዎቹ የእውቅና ሰርተፍኬት በመስጠት እንዲሁም በኢትዮ ቴልኮም ድጋፍ ከአንድ እስከ ሶስት በመውጣት ላሸነፉት ተወዳዳሪዎች ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ እምቅ አቅም ያላቸውን ታዳጊዎችና ወጣቶች ለማበረታታት መሰል ዝግጅቶች ወደፊት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በመግለጽ አውደርእዩ በይፋ ዘግተዋል።