የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች እና የተጠሪ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ህዳር 10/2014 ዓ.ም በመገኘት ጉብኝት አደረጉ፡፡
የባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ዋና ዳይሬክተር ኤርምያስ የማነብርሃን (ዶ/ር) የተቋሙን ኃላፊነትና ተግባር፣ አንኳር አፈጻጸሞች፣ ተግዳሮቶች እና የወደፊት አቅጣጫን በማስመልከት ገለጻ አቅርበዋል፡፡ ክቡር ሚኒስትርና ከፍተኛ አመራሮች የባለስልጣን መስሪያ ቤቱን የተለያዩ ክፍሎች በመዘዋወር ጉብኝት አድርገዋል፡፡
የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እና የተጠሪ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች በቀረበላቸው ገለጻና በጉብኝት ወቅት የታዘቡዋቸውንና ግልጽ ያልሆኑ ጉዳዮች በማስመልከት አስተያየትና ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ የዜጎችን የአእምሮ ውጤት የሆኑ የፈጠራ ስራዎችን በማስጠበቅና በማልማት ሀገራችን ለተለመችው ዕድገት አበርክቶ እንዲኖራቸው ጠንካራ የአእምሯዊ ንብረት ስርዓት መገንባት እንደሚገባ አመራሮቹ አመላክተዋል፡፡ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በዘርፉ የተጣለበትን ኃላፊነት መወጣት እንዲችል በበጀት እና በመሰረተ ልማት ግንባታ ሊታገዝ እንደሚገባውም አክለው ገልጸዋል፡፡
ክቡር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር ዜጎች ከፈጠራ ስራዎቻቸው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ተቋሙ የጀመረውን ተግባራት ማጠናከር እንደሚገባውና ለዚህም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል፡፡ የአእምሮ ውጤት የሆኑ የፈጠራ ስራዎች እውቅናና ጥበቃ ካላገኙ የማህበረሰብ ለውጥ ማምጣትና የሀገር እድገት ማስመዝገብ እንደማይቻል አክለው ገልጸዋል፡፡