ጽ/ቤቱ የአዕምሯዊ ንብረት ሕጎች ህጋዊ ተፈፃሚነትን አስመልክቶ ከፌደራል እና ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን፣ ከየክፍለከተሞቹ የፖሊስ መምሪያ ከሚገኙ አባላት ከንግድ ውድድርና ሸማቾች ባለስልጣን ዕንባ ጠባቂ ተቋም ከተወከሉ ባለሙያዎች ጋር በቢሾፍቱ ከተማ ጥር 6/2013 ዓ.ም ውይይት አካሄደ ።
የጽ/ቤቱ ም/ዋና ዳይሬክተሩ እንዳለው ሞሲሳ የውይይቱን ዓላማ ሲገልጹ የአእምሯዊ ንብረት ሕጎች ጥሰትን ለመከላከል በቅንጅት መሥራት አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነ አስታውሰዋል፡፡
ጽ/ቤቱ በአዋጅ ቁጥር 325/95 በይፋ ራሱን ችሎ ከመቋቋሙ በፊት በተለያዩ ሚንስቴር መሥሪያ ቤቶች አገልግሎቱን ይሰጥ እንደነበር ገልፀው፣ ሌሎች መንግስታዊ ተቋማት አንድ አዋጅን ሲያስጠብቁ አእምሯዊ ንብረት በርካታ አዋጆችን በማስጠበቅ ከሌላው ተቋም በተለየ መልኩ ስራውን እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፤ ይህን በሕገመንግስቱ እና በማቋቋሚያ አዋጁ ያለውን ስልጣንና ኃላፊነት ለመተግበር የሕግ አካላት ጋር ተቀናጅቶ መሥራት ወሳኝ መሆኑን አብራርተዋል ።
የአእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት የሕግ ክፍል ከፍተኛ ባለሙያ ደረጀ ጽጉ የአእምሯዊ ንብረት እንደሌሎቹ ሀብቶች የሚጨበጥና የሚዳሰስ ባለመሆኑ ለጥሰት እንደሚጋለጥ አብራርተው በተለይ በንግድ ምልክት ላይ የሚያጋጥሙንን ማጭበርበር በምሳሌ በማቅረብ አብራርተዋል፡፡ በመቀጠልም የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን የሚያስገኘውን ጥቅም አስመልክቶ መንግስት እያጣ ያለውን የገቢ መጠን አስረድተው ይህንን ለመለወጥ በቅንጅት መሥራት እንደሚገባ አስረድተዋል።
የአእምሯዊ ንብረት ትሪቢውናል ኃላፊ አብርዱ ብርሀኑ የስራ ክፍሉ ከጳጉሜ 1//2010 በፊት በኮሚቴ እየተሰራ እንደነበር ገልጸው በስራ ክፍል ደረጃ ለመመሥረት ገፊ ምክንያት የሆነው በጽህፈት ቤቱ የሚስተናገዱ ደንበኞች ቅሬታ እየጨመረ በመምጣቱ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ተሳታፊዎቹም ውይይቱ ወቅቱን የጠበቀ መሆኑን ገልጸው የተለያዩ መብራራት ያለባቸውን ጥያቄዎች አንስተው ጽሑፍ አቅራቢዎቹና ከጽ/ቤቱ ባለሙያዎች ምላሽ ተሰጥቷቸዋል።