ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በአእምሯዊ ንብረት ጽንስ ሃሳብ፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር እና በጋራ በሚሰሩ ስራዎች ዙሪያ ከናይስ ኢኖቬሽን ኢንኩቤሽን፣ ከአይስ አዲስ ኢንኩቤሽን፣ ከኤክስ ሃብ አዲስ ኢኩቤሽን ማዕከላት ለተውጣጡ ባለሙያዎችና ኃላፊዎች እንዲሁም በማዕከላቱ ተጠቃሚ ለሆኑ የፈጠራ ባለሙያዎች ዛሬ መጋቢት 15/2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስልጠና ሰጠ፡፡
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኤርምያስ የማነብርሃን (ፒኤችዲ) መድረኩን በከፈቱበት ወቅት የኢንኩቤሽን ማዕከላት የፈጠራ ሃሳብ ያላቸው ሰዎች ስራዎቻቸውን ወደ ተግባር እንዲቀይሩና ከስራዎቻቸው ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ ረገድ ሚናቸው የጎላ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የአእምሯዊ ንብረት ጽንስ ሃሳብንና የጥበቃ ስርዓትን በመገንዘብና በማስገንዘብ እንዲሁም ዘርፉን የዕድገት አንቀሳቃሽ መሳሪያ በማድረግ ረገድ በቅንጅት መስራት እንደሚገባም አክለው ገልጸዋል፡፡
የቴክኖሎጂ ሽግግርና ማማከር ቡድን መሪ ስንታየሁ ታደሰ ለኢንኩቤሽን ማዕከላቱ ባለሙያዎች የተዘጋጀው ስልጠና በአእምሯዊ ንብረት ጽንስ ሃሳብና ከኢንኩቤሽን ማዕከላቱ ጋር በጋራና በቅንጅት ሊሰሩ በሚገባቸው ተግባራት ዙሪያ ለመወያየት የተዘጋጀ መድረክ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የኢንኩቤሽን ማዕከላቱ የንግድ ስራ ሃሳብ እንዲሁም የፈጠራ ስራ ሃሳብ ያላቸው ሰዎች በተለያዩ ቁሳቁሶች በማገዝ ስራዎቻቸውን ወደ ተግባር እንዲለወጡና ወደ ገበያ እንዲያወጡ የማድረግ ሃላፊነት ያለባቸው በመሆኑ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ወጣቶችንና የፈጠራ ባለመብቶችን ለመደገፍ የሚያደርገውን ስራ እንደሚያጠናክር አክለው ጠቅሰዋል፡፡
ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በፓተንት የታቀፉ የቴክኖሎጂ መረጃዎችና የምርምር ጆርናሎች ልውውጥ ለማድረግ፣ የፈጠራ ባለመብቶች ስራዎቻቸውን ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚያደርጉትን ስራ ለመደገፍ፣ በአእምሯዊ ንብረትና በኢንተርፕርነርሺፕ ግንዛቤ ፈጠራ ላይ በጋራ ለመስራት እን በሌሎች ጉዳዮች ላይ በጋራ መስራት በሚቻልበት አግባብ ላይ ውይይት ተደርጓል፡፡
የስልጠናው ተሳታፊዎች በአእምሯዊ ንብረትና በቅንጅት በሚሰሩ ተግባራት ዙሪያ የተለያዩ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን አንስተው ውይይት ተደርጎበታል፡፡
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አማካሪና የፓተንት ጥበቃና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር ፍሬው ገላው የባለስልጣን መስሪያ ቤቱና የኢንኩቤሽን ማዕከላቱን ተግባርና ኃላፊነት የሚያሳይ የጋራ መግባቢያ ሰነድ በመፈራረም በቀጣይ ስራዎችን በጋራ መስራት እንደሚገባ በውይይቱ ማጠቃለያ ላይ ተናግረዋል፡፡